Monday, December 29, 2014

‹‹ላቆምከው ምስል አንሰግድም ››



 
 ‹‹የእግዚአብሔር መልአክ በአምላኩ ፊት ቆሞ ሰባ አመት በባቢሎን ምድር ተቆጠሃቸዉ ዕብራዉያንን የማትምራቸዉ እስከመቼ ነዉ? ብሎ ጸለየ እግዚአብሔርም የመልአኩን ጸሎት ተቀብሎ በሚያጽናና ቃል እስራኤልን በምህረት የምጎበኝበት ጊዜ ደርሷል አለዉ፡፡›› ዘካ1፤12

መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል
ዕብራውያን ሲበደሉ እግዚአብሔር በተለያየ መንገድ ይገስጻቸው ነበር፡፡ 430 ዓመታት በግብጽና በቃዴስ በርሐ 70 ዓመት በባቢሎን ሲጨቆኑ እና መከራቸውን ሲያዩ ተስፋ ቆርጠው እግዚአብሔር የለም እስከማለት እንዳይደርሱ እነ ሙሴን፣ ኤርሚያስን፣ዳንኤልንና ሠለስቱ ደቂቅን  በመካከላቸው እንዲኖሩ አደረገ፡፡ ዕብራውያን ለዘመናት በባቢሎን ምድር በግዞት ሳሉ አናንያ፣አዛርያና ሚሳኤል ከዳንኤል ጋር በዚያ ነበሩ፡፡ንጉስ ናቡከደነጾር የባቡሎንን ጥበብ እንዲማሩ የተለየ እንክብካቤ ያደርግላቸው ነበር፡፡ እነዚህ ሦስቱ ወጣቶች የቀረበውን ጠጅና ስጋ ከመመገብ ይልቅ እፍኝ የምታህል ጥሬና ጥቂት ውሃ እየተጎነጩ በጾምና በጸሎት በስግደት እንዲወጡ እግዚአብሔርን ይለምኑት ነበር፡፡በሚመገቡት ምግብ ያልተደሰቱ የባቢሎን ጠቢባን ‹‹ሰውነታችሁ ገርጥቶ ብትገኙ ንጉስ ከፍ ብሎ አንገታችን ዝቅብሎ ባታችንን ይቆርጠናል፡፡እባካችሁ ሰውነታችሁ እንዲፋፋ ስጋውን ብሉ ጠጁን ጠጡ›› እያሉ ይለምኗቸው ነበር፡፡ወጣቶቹ በጾምና በጸሎታቸው ምክንያት ምንም ዓይነት አካላዊ ጉዳት እንዳይደርስባቸው አበክረው ይነግሯቸ ነበር፡፡በደስታቸው ጊዜ ያልተለያቸው እግዚአብሔር በባዕድ ምድር በአህዛብ መካከል ከፍ ከፍ አደረጋቸው፡፡ጥበባቸውና ዝናቸው በዓለሙ ሁሉ ተሰማ ፤ንጉሱም ስለ አስተዋይነታቸው በሦስቱ የባቢሎን አውራጇዎች ሾማቸው፡፡ይህ ሹመት ያናደዳቸው የባቢሎን የጥበብ ሰዎች ‹‹እኛ እያለን እነዚህ ስደተኞች ትናንት መጥተው መሾማቸው ከየት የመጣ ነው፡፡›› ብለው ከንጉሱ ጋር የሚጣሉበትን ነገር መንገድ ይፈልጉ ጀመር፡፡በየእለቱ ምክንያት ለማግኘት ቢከታተሏቸውም ምንም ዓይነት ጉድለት ማግኘት ስላልቻሉ በጣም አዝነው እየተቆጩ ‹‹እነዚህ ዕብራውያን ከአምካቸው በቀር ምክንያት ልናገኝላቸው አልቻልንም›› ብለው ተስፋ ቆረጡ፡፡ሦስቱ የባዕድ ሀገር ልጆች በህይወታቸ እግዚብሔርን እያከበሩ ይኖሩ ነበር፡፡ነበዩ ዳንኤልም የጸሎት ቤቱን መስኮት በአንጻረ ኢየሩሳሌም ከፍቶ ይጸልያል፡፡መማክርቱ ወደ ናቡከደነጾር ገብተው ‹‹ንጉስ ሆይ አንተ የሾምካቸው ሦስቱ ዕብራውያን ያንተን አምላክ ከማምለክ ተከለከሉ ምን ይሻላል›› ብለው አማከሩት፡፡ንጉሱም ጣዖቱ የተናቀ መስሎት ግራ ገባው፡፡መማክርቱም  ‹‹ንጉስ ሆይ አትጨነቅ በዱራ ሜዳ ላይ የምታመልከውን የወርቅ ምስል አቁም ህዝቡምና ሁሉ ላቆምከው ምስል ይስገድ፤እውነት እነዚህ ልጆች ልባቸው ከአንተ ጋር ከሆነ አንተ ላቆምከው የወርቅ ምስል ይሰግዳሉ›› አሉት፡፡ናቡከደነጾር በዚህ ምክር ተስማምቶ ቁመቱ 30 ወርዱ 3ሜትር የሆነ  የወርቅ መስል አቆመ፡፡ንጉሱ ላቆመው ጣኦት የእምቢልታ የመሰንቆ የክራር የበገናና የዋሽንት ድምጽ በተሰማ ጊዜ ህዝቡ እንዲሰግድ አዋጅ ተነገረ፡፡በዚህ ጊዜ የእምነት አርበኞች የእውነት ምስክሮች በባቢሎን ምድር የፈኩ ዕንቁዎች አናንያ፣አዛርያና ሚሳኤል ለንጉሱ ‹‹እኛ አንተ ላቆምከው ምስል አንሰግድም እግዚአብሔር ከሚነደው እሳት ያድነናል፤ባያደነንም እንኳን/እርሱ ፈቅዶ በሰማዕትነት ብናልፍ/ አንተ ላቆምከው ለወርቅ ምስል አንሰግድም፡፡ብለው ቁርጡን ነገሩት፡፡‹‹ይህ ባታደርጉ በእሳት እንድትቃጠሉ ወደ እቶን እጥላችኋላው››አላቸው፡፡እነርሱም በእምነት ያለጥርጥር ‹‹የምናመልከው አምላክ ከሚነደው እሳት ሊያወጣን ይችላል›› አሉት፡፡በሁኔታቸው እጀግ የተቆጣው ናቡከደነጾር እሳት አስነድዶ ወደ እቶን እንዲገቡ አዘዘ፡፡አናንያ፣አዘርያና ሚሳኤል ከእሳቱ ውስጥ ሁነው ‹‹ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ ተብለህ በምትመሰገን በጽርሐ-አርያም የከበርክ ነህ፤ እግዚአብሔር ከሞትን ከሲኦል እጅ አድኖናልና ከነበልባሉ መካከል አውጥቶናልና ለእግዚአብሐር ተገዙ ስሙን አመስግኑት እያሉ ያመሰግኑ ነበር፡፡እግዚአብሔርም መላእኩን ላከ፡፡ሊቀ መላእክት ቅዱስ ገብርኤል የሚነደዉን እሳት በመስቀል ቢባርከዉ እሳቱ እንደ ዉሃ ቀዘቀዘ፡፡




ንጉስ ናቡከደነጾርም ሦስቱ ህጻናት የሚነደዉ እሳት ‹‹አቃጥሏቸዋል? ወይስ የሚያመልኩት አምላክ አድኗቸዋል?››ብሎ ሊያረጋግጥ ወደ እሳቱ ተጠጋ መልአክ በሦስቱ ልጆች መካከል ቆሞ ሲያረጋጋቸዉ ታየ ንጉሱም ሦስት ሰዎች ወደ እሳት ጥለን ነበር፤አሁን አራት ሰዎችን አያለሁ ይልቁንም አራተኛዉ ሰዉ የእግዚያብሔር ልጅ ይመስላል ብሎ በመደነቅ መሰከረ፤ሦስቱ ህጻናት ግን አይደለም ሊቃጠሉ የቀሚሳቸዉን ዘርፍ ሳይነካ ከእሳት ሲወጡ ሊቀመላእክት ቅዱስ ገብርኤል ወደሰማይ አረገ በመጨረሻም ንጉሱ ለሦስቱ ህጻናት አምላክ ያልሰገደ ቢቱ የጥራጊ መጣያ ይሆናል፡፡አዋጁን ለወጠ በሦስቱ ህጻናት ላይ የነደደዉ እሳት ዛሬ መልኩን፡ቀይሮ፤ህይወታችንን፡ከበቧል፡፡ክርስቲያዊ ህይወታችንን የሚያበላሹ በዙሪያችን የተሰደሩ የሀጢያት፡ወላፈኖች ቅዱስ ጳውሎስ፤እንደጻፈልን የዝሙት፣ የርኩሰት፣ የመዳራት፣ ጣኦትን የማምለክ፣የሟርት፣የጥል፣የክርክር፣የቅንአት፣የቁጣ፣የመለያየት፣የመናፍቅነት፤የስካር፣የዘፋኝነት፡ናቸዉ፡፡/ገላ፭፤፲፱/ በአርያውን በአምሳሉ ከፈጠረን የዘለዓለምን ህይወት ካደለን ከሰማይ አምላክ ከእግዚአብሔር በቀር ሌላ አምላክ የለምና ዛሬም እንደጥንቱ ለቆመው ሐውልት ስገዱ ብንባል እንደ አባቶቻችን የምናወድሰው፣የምንዘምረው፣ቅዳሴና፤ማኅሌን፤አኮቴትና ቁርባኑን፣ሰጊድና አምኃውን የምቃርበው ለእግዚአብሔር ብቻ ነው፤ልንል ይገባናል፡፡ስለዚህ ዉድ ምእመናን ማስተዋልን ገንዘብ ማድረግ ይጠበቅብናል፡፡
ደብረ ምህረት አቡን ቤት ቅዱስ ገብርኤል ሰንበት ት/ቤት ታህሳስ/2007ዓ/ም



No comments:

Post a Comment

ደ/ም/አ/ቤ/ቅ/ገ/ሰ/ት/ቤት ጎንደር